የንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት የብር ለውጡ የአንድ ወር የጊዜ ገደብ እንዲበጅለት ጠየቁ

የንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት የብር ለውጡ የአንድ ወር የጊዜ ገደብ እንዲበጅለት ጠየቁ
Sep 16, 2020

የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ አቤ ሳኖ አዲስ የታተሙት ብሮች ወደ ገበያ ገብተው አሮጌዎቹ ብሮች ሙሉ ለሙሉ የሚተኩበት የጊዜ ገደብ፣ ከሦስት ወራት ወደ አንድ ወር እንዲያጥር ጠየቁ፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ አዲስ 200 የብር ኖት ማምጣቱንና 100 50 እና የአሥር ብር ኖቶች ላይም ቅያሪ ማድረጉን ይፋ ባደረገበት መድረክ ሰኞ መስከረም 4 ቀን 2013 .. ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት አስተያየታቸውን የሰነዘሩት አቶ አቤ፣ የሦስት ወራት የጊዜ ገደብ የተቀመጠለት የመቀየሪያ ጊዜ ረዥም ስለሆነ አንድ ወር ብቻ በቂ ነው ብለዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞ 100 ሺሕ ብር በላይ ያለባቸው የተቀመጠው የአንድ ወር የመቀየሪያ ጊዜ ቢበዛ በሁለት ሳምንት፣ ከተቻለም በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ መቀየር እንዲቻል ጊዜው ቢያጥር ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

በተጨማሪም በጥሬ ገንዘብ ከአሥር ሺሕ ብር በላይ ይዞ ወደ ባንክ ለመቀየር የሚመጣ ማንኛውም  ሰው የባንክ አካውንት መክፈት እንዳለበት የተላለፈው ውሳኔ፣ ከአምስት ሺሕ ብር ጀምሮ ይዞ በሚመጣ ሰው ላይ ተግባራዊ እንዲደረግ ሲሉም ጠይቀዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (/) የተነሱትን ጥያቄዎች አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ፣ ይኼ የጊዜ ገደብ የተቀመጠው ባንኮች ሥራ ስለሚበዛባቸውና በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ ቀይረው ያገባዱ ሲባል ሊከብዳቸው ይችላል በሚል ዕሳቤ ነው ብለዋል፡፡ በዚህም መሠረት ሦስት ወራት እንዲሆን እንደተወሰነ በማስታወቅ፣ ባንኮቹ እንችላለን ካሉ ግን በአንድ ወር ውስጥ እንዲጨርሱ ከብሔራዊ ባንክ ጋር ውይይት እንዲደረግ አሳስበዋል፡፡

የብር ለውጡን ለማድረግ ዋናው ምክንያት ከሁለት ዓመታት ወዲህ በአገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ ለመለወጥ እየተሞከረ ያለውን የኢኮኖሚ ስብራት መጠገን እንደሆነ የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ከለውጡ በኋላ በተደረገ ዳሰሳ ኢኮኖሚው ከፍተኛ የሆነ የማክሮ ኢኮኖሚ ማዛባት እንዳለበት በመረጋገጡ ቁልቁል ሲሄድ የነበረውን ኢኮኖሚ  ማስቆም ዋናው ዓላማ ነው ብለዋል፡፡

የብር ኖቶቹን መቀየር አስፈላጊነት አክለው ያስረዱት የብሔራዊ ባንክ ገዥ ይናገር ደሴ (/) በበኩላቸው፣ ኖቶቹን መቀየር ያስፈለገባቸው በርካታ ምክንያቶች እንዳሉት ተናግረዋል፡፡ የመጀመርያው ምክንያት በርካታ ገንዘብ ከባንክ ውጪ በመኖሩ ሕገወጥ ተግባራት፣ ሙስናና ኮንትሮባንድ ስለተስፋፉ ያንን ለመከላከል ነው ብለዋል፡፡  ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ ባንኩና ውጪ ያለ ገንዘብ ሲበራከት የጥሬ ገንዘብ እጥረት ስለሚያጋጥማቸው ያንን ለመከላከል  ታስቦ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

ሌላው ምክንያት ደግሞ የገንዘቦቹን የደኅንነት መጠበቂያ ማሻሻያ ሲሆን፣ ከአሁን ቀደም በእነዚህ የደኅንነት ጠበቂያዎች ላይ ጉልህ ማሻሻያ ባለመደረጉ ለሐሰተኛ ህትመትና ሥርጭት ተጋላጭ ሆነዋል ሲሉም አስረድተዋል፡፡

ለገቢ አሰባሰብ ምቹ ሁኔታን ለመፍጠር ያለው ጥቅም ሌላው የተገለጸ ምክንያት ሲሆን፣ ሰዎች ያላቸው የገንዘብ መጠን በባንክ ሲዘዋወር ምን ያህል ሀብት እንዳላቸውና ምን ያህል ታክስ መሰብሰብ እንዳለበት ለማወቅ ይቻላል ብለዋል፡፡

ከዚህ በተጨማሪም አሁን የተደረገው ቅያሪ 200 ብር ኖት በማስተዋወቁ ትልልቅ ገንዘቦችን ማተም የኅትመት ወጪ ለመቀነስ እንደሚረዳ ገልጸው፣ የጥሬ ገንዘብ  ዝውውር ለመቀነስ ያግዛል ሲሉም አክለዋል፡፡

አሁን የታተመው የገንዘብ መጠን 262 ቢሊዮን ብር መሆኑን፣ የታተመው ኖት ደግሞ በቁጥር 2.9 ቢሊዮን እንደሆነ ይናገር (/) ለሪፖርተር ተናግረው፣ ለብር ኅትመቱ 3.7 ቢሊዮን ብር ወጪ መደረጉንም ገልጸዋል፡፡

ይኼ የብር ለውጥ ፕሮጀክት ኤክስ (X) ተብሎ በሚስጥር ሲሠራበት መቆየቱን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ የኮሚቴውን አባላት አመሥግነዋል፡፡